29/04/2026
#የኢትዮጵያ የባሕር ትራንስፖርትና ሎጀስቲክስ የ2018/19 የምርት ዘመን ማዳበሪያ አቅርቦትን በተያዘው የበጀት ዓመት ዘጠኝ ወራት ብቻ 1 ሚሊየን 556 ሺህ 157 ቶን በማጓጓዝ ለግብርናው ዘርፍ ያለውን ቁርጠኝነት አረጋግጧል።
የኢትዮጵያ የባሕር ትራንስፖርትና ሎጀስቲክስ በበጀት ዓመቱ የዘጠኝ ወራት አጠቃላይ የኦፕሬሽን አገልግሎቱን በማሳደግ የዕቅዱን 109 በመቶ ማሳካት የቻለ ሲሆን፣ ይህም ካለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነፃፀር የ22 በመቶ ብልጫ ያለው ነው።
ይህ ስኬት በተለይ እንደ ማዳበሪያ ያሉ ስትራቴጂካዊ የሀገር ውስጥ ግብዓቶች ሳይስተጓጉሉ ወደ ተጠቃሚው እንዲደርሱ በማድረግ ረገድ ፋይዳው የጎላ ሲሆን ከአገልግሎት አሰጣጥ ፍጥነት አንጻርም በጂቡቲ ወደብ የኮንቴይነር ቆይታን ለማሳጠር በተደረገው ጥረት፣ የቆይታ ጊዜውን ከታቀደው 7 ቀን ወደ 4.89 ቀናት ዝቅ ማድረግ ተችሏል።
ይህም እንደ ማዳበሪያ ያሉ ወቅታዊ ግብዓቶች በፍጥነት ተጓጉዘው ለገበሬው እንዲደርሱ ምቹ ሁኔታን ከመፍጠሩ በተጨማሪ ድርጅቱ መንግስት የግብርና ምርታማነትን ለማሳደግ ያስቀመጠውን አቅጣጫ በመከተል፣ ለግብርና ስራዎች ኮርፖሬሽን ከሚሰጠው የየብስ ትራንስፖርት አገልግሎት ጋር በተያያዘ ከ28.1 ቢሊየን ብር በላይ የሚገመት የትራንስፖርት አገልግሎት በማቅረብ ላይ ይገኛል።
የኢትዮጵያ የባህር ትራንስፖርትና ሎጅስቲክስ በቀጣይም ዘመናዊ፣ ቀልጣፋና ወጪ ቆጣቢ የሆነ የሎጅስቲክስ አገልግሎትን በማቅረብ የሀገሪቱን የምግብ ዋስትና ለማረጋገጥ የሚደረገውን ጥረት በላቀ ደረጃ ለመደገፍ በትኩረት እየሰራ ይገኛል።