23/05/2026
ከኮንቴነር ባሻገር፤
ኢትዮ- ጅቡቲ ባቡር በሎጂስቲክስ ዘርፉ በመደበኛነት ጥቅም ላይ የሚውሉ የኮንቴነር አይነቶችን ማለትም ባለ 20 እና 40 ጫማ ኮንቴነሮችን (20 ft and 40 ft containers) በመጠቀም የገቢና ወጪ ጭነቶችን በማጓጓዝ ጉልህ ድርሻ እያበረከተ ይገኛል።
በኮንቴነር የሚጓጓዙ ጭነቶችን ምቹና ቀልጣፋ ለማድረግ በዲጂታል አማራጭ የታገዘ አገልግሎት በመስጠት እና የኮንቴነር ማራገፊያ ደረቅ ወደቦችን በማደራጀት ወደ ግዙፍ የሎጂስቲክስ ማዕከልነት ተሸጋግሯል።
የሀገራችን ወጪና ገቢ ቁሳቁሶች በመጠንና በዓይነት ዕድገት ማስመዝገባቸውን ተከትሎ በኮንቴነር ብቻ ተገድቦ የቆየውን አገልግሎት ማስፋት አስፈላጊ ሆኖ በመገኘቱ የተለያዩ ጭነቶችን በማጓጓዝ አዲስ ምዕራፍ ከፍቷል። ይህ የሎጂስቲክስ ስትራቴጂካዊ ለውጥ የጭነት አቅማችንን በእጅጉ አሳድጎታል።
በዚህም የቁም እንስሳት ፣ ግዙፍ ማሽነሪዎች፣ በኤሌክትሪክ ኃይል የሚሰሩ የጭነትና አነስተኛ የቤት አውቶሞቢሎች፣ የኤሌክትሪክ አውቶብሶች፣ የዓለምአቀፉ ደረጃዎች ድርጅት (ISO) መስፈርቶችን ያሟሉ የዘይት ኮንቴይነሮችን በማጓጓዝ የሎጂስቲክስ ዘርፉ ላይ ተጨባጭ ለውጦችን ማስመዝገብ ችለናል።
እነዚህ ጭነቶች በሀገራችን እየተከናወኑ ለሚገኙ የልማት ስራዎች ሁነኛ ግብአት በመሆናቸው በፍጥነት ከወደብ በማንሳትና ወደ መዳረሻቸው በመውሰድ የሚጠበቅባቸውን አገልግሎት እንዲሰጡ ማድረግ ተችሏል።
ግመሎችን ጨምሮ የቀንድ ከብቶችን በባቡር የማጓጓዝ ስራ መጀመሩ ሀገራችን ከዘርፉ ማግኘት የሚገባትን ጥቅም በተሻለ መንገድ እንድታገኝ አስችሏል።
በኤሌክትሪክ ኃይል የሚሰራው የባቡር መስመሩ 'አረንጓዴው ባቡር ለአረንጓዴ ትራንስፖርት' በሚል መሪ ሃሳብ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎችን በማጓጓዝ ሀገራችን ለተያያዘችው የማይበገር የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ግንባታ ዕውን መሆን የበኩሉን ድርሻ እየተወጣ ነው።
ከኮንቴነር ጭነት ባሻገር የባቡር ጭነት ዓይነቶችን በመጠንና በዓይነት በማስፋት ፈጣን፣ አስተማማኝ እና ወጪ ቆጣቢ የሎጂስቲክስ አገልግሎትን የማላቅ ተግባራችን ይበልጥ ተጠናክሮ ይቀጥላል።