06/08/2026
አገልግሎቱ የ2018 ዓ.ም እቅድ አፈፃፀምን ገምግሞ የ2019 እቅድን አስተዋወቀ//
የፐብሊክ ሰርቪስ ትራንስፖርት አገልግሎት ሀምሌ 30 ቀን 2018 ዓ.ም ከህዝብ ክንፍ አባላት፣ ከመንግስት ተቋማትና ከሌሎች ባለድርሻ አካላት ጋር የ2018 በጀት ዓመት እቅድ አፈፃፀም እና የ2019 በጀት ዓመት እቅድ በተመለከተ ሰፊ የግምገማና የውይይት መድረክ እንዲሁም የእውቅና ፕሮግራም አከናወነ።
የፐብሊክ ሰርቪስ ትራንስፖርት አገልግሎት ዋና ዳይሬክተር ወ/ሮ አስካለ ተክሌ ከህዝብ ክንፍና ከባለድርሻ አካላት ጋር ትውውቅ ካደረጉ በኋላ ፕሮግራሙን በንግግር ከፍተዋል፡፡
ዋና ዳይሬክተሯ በመክፈቻ ንግግራቸው የ2018 ዓ.ም በጀት ዓመት እቅድ አፈፃፀምን መገምገም ያለፈውን ለመተንተን ብቻ ሳይሆን ከተገኙ ጥንካሬዎችና ድክመቶች በመማር የ2019 በጀት ዓመት ስራዎችን በተሻለ መልኩ ለማሳካት የሚያግዝ መሆኑን ገልጸው የህዝብ ትራንስፖርት አገልግሎት የከተማዋን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴ የሚደግፍ መሰረታዊ አገልግሎት በመሆኑ ጥራቱን፣ ተደራሽነቱንና ቀልጣፋነቱን ማሳደግ የሁሉም ባለድርሻ አካላት የጋራ ኃላፊነት መሆኑን አስገንዝበዋል።
በተጨማሪም በ2019 በጀት ዓመት የተቀመጡ እቅዶችን ለማሳካት የህዝብ ክንፍ፣ የመንግስት ተቋማት፣ የጸጥታና የትራፊክ ቁጥጥር አካላት እንዲሁም ሌሎች ባለድርሻ አካላት ያላቸው ተሳትፎ ትብብር ወሳኝ መሆኑን ጠቁመዋል።
የአገልግሎቱ የእቅድና ገበያ ጥናት ዳይሬክቶሬት ቡድን መሪ የሆኑት አቶ መክዩ አክመል ባቀረቡት ሪፖርት በ2018 በጀት ዓመት የተከናወኑ ዋና ዋና ስራዎች፣ የተመዘገቡ ውጤቶች፣ ያጋጠሙ ተግዳሮቶችና ከእነዚህ የተገኙ ተሞክሮዎች በዝርዝር ቀርበዋል::
በተጨማሪም በ2019 በጀት ዓመት የአገልግሎት ጥራትን ማሻሻል፣ የህዝብ እርካታን ማሳደግ፣ ተቋማዊ አቅምን ማጠናከር እና ከባለድርሻ አካላት ጋር ያለውን ትብብር ይበልጥ ማጎልበት በዋናነት ትኩረት እንደሚሰጣቸውም ተገልጸዋል።
የዲጂታል መታወቂያ አጠቃቀምን በተመለከተ በአገልግሎቱ የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር በወ/ሮ ሰሚራ ሁሴን ማብራሪያ ተሰጥቶበታል፡፡
ውይይቱን የመሩት የአገልግሎቱ ዋና ዳይሬክተር ወ/ሮ አስካለ ተክሌ እና የትራንስፖርት አገልግሎት ዘርፍ ምክትል ዋና ዳይሬክተር ወ/ሪት ቤዛዊት ተሾመ እንዲሁም የሀብት ምደባና አጠቃቀም ዘርፍ ም/ዋና ዳይሬክተር አቶ ዘውዱ አሰፋ ሲሆኑ በቀረበው ሪፖርትና እቅድ ዙሪያ ከተሳታፊዎች ለተነሱጥያቄዎች ሀሳቦችና አስተያየቶችምላሽና ማብራሪያ ሰጥተዋል፡፡
ተሳታፊዎችም በቀረበው ሪፖርትና በቀጣዩ ዓመት እቅድ ላይ ገንቢ አስተያየቶችን በማቅረብ በተቀናጀ አሰራር የተሻለ የህዝብ ትራንስፖርት አገልግሎት ለመስጠት በጋራ እንደሚሰሩ አረጋግጠዋል።
በመድረኩ መጨረሻ በ2018 በጀት ዓመት የላቀ አፈፃፀም ላሳዩ ለ11 ክፍለ ከተሞች የትራፊክ ቁጥጥር መምሪያ እና ለመንግስት ተቋማት እንዲሁም ለኮማንድ ፖስት አባላት የእውቅና የምስክር ወረቀት ተሰጥቷል፡፡